መስከረም 26/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) ‎ሁለተኛው ዓለም አቀፍ የጤና እንክብካቤ ኮንፈረንስ "በ21ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመሪያ ደረጃ የጤና እንክብካቤን ማሳደግ እና ሰውን ማስቀደም" በሚል መሪ ቃል ከ64 በላይ ሀገራት የተውጣጡ ተሳታፊዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ በዓድዋ ሙዚየም በመካሄድ ላይ ይገኛል።

በኮንፍረንሱ ገለጻ ያደረጉት የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ ኢትዮጵያ ባለፉት 20 ዓመታት የዜጎችን ጤና የሚያሻሽሉ ሥራዎችን ተግባራዊ ስታደርግ መቆየቷን ጠቁመው፤ በዚህም በዓለም አቀፍ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ላይ እንድትሆን ማስቻሉን አብራርተዋል።

Post image

በዚህም ሂደት የእናቶችን የወሊድ ሞት ምጣኔ በመቀነስ እና የጤና ተቋማት ተደራሽነትን በማስፋፋት ሥራ የመጀመሪያ ደረጃ ጤና ክብካቤ አስተዋጽኦ የጎላ ስለመሆኑ ጠቁመዋል።

ከአጋር እና ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የሕብረተሰቡን ፍትሐዊ የጤና ተጠቃሚነት ለማስፋትም የተለያዩ ለውጦች መተግበራቸው ይቀጥላል ነው ያሉት።

የመጀመሪያ ደረጃ ጤና ክብካቤ በጤናው ዘርፍ ብቻ ሳይሆን የመንግሥት የልማት ግብ አጀንዳ ተደርጎ እየተሠራበት ይገኛል ሲሉም ገልጸዋል።

የእናቶችና ሕጻናት ሞት ቅነሳ እንዲሁም በበሽታ ቅድመ መከላከል በኩል ለውጥ መምጣቱን ገልጸው፤ በጤና ኢንቨስትመንት ትኩረት የተሰጠው የመሰረተ ልማት ግንባታም እየተስፋፋ መሆኑን ተናግረዋል።

Post image

የዓለም አቀፉ የመጀመሪያ ደረጃ ጤና ክብካቤ በኢትዮጵያ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አብነት ዘለቀ በበኩላቸው፤ ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ የመጀመሪያ ደረጃ ጤና ክብካቤን ለማኅበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት ሲተገበር መቆየቱን አብራርተዋል።

በዚህም በመረጃ ላይ የተመሠረተ የጤና ሥርዓትን መገንባት፣ የውስጥ ፖሊሲዎችን ማሻሻል፣ የጤና ባለሙያዎችን አቅም ማጎልበት እና ማኅበረሰብ ተኮር የጤና ተደራሽነትን ማስፋት ላይ ውጤታማ ሥራ መሥራት ተችሏል ብለዋል።

ኮንፈረንሱ ከሃሳብ ልውውጥ የተሻገረ አጋርነትን በመመሥረት ዘላቂ የጤና ክብካቤን ለመተግበር መንቀሳቀስ ይገባልም ሲሉ አሳስበዋል።

ሀገራት የጤና ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የመጀመሪያ ደረጃ የማኅበረሰብ ጤና ክብካቤ ላይ ትኩረት አድርገው መሥራት እንደሚጠበቅባቸውም በመድረኩ ተመላክቷል።

በኮንፈረንሱ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ ከ705 በላይ ተሳታፊዎች የተገኙ ሲሆን፤ ለተከታታይ አምስት ቀናት በተለያዩ ሁነቶች የሚቀጥል ይሆናል።

#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ