ሕዳር 16/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) እንደ ሀገር ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች የሚጠቁ ዜጎች ቁጥር መጨመሩን ጤና ሚኒስቴር ለአሐዱ ሬዲዮ አስታውቋል።

በጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጄ ድጉማ፤ በኢትዮጵያ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መጨመራቸውን ተከትሎ ስጋት መደቀኑን ጠቁመዋል።

ተላላፊ በሽታዎች እንደ ሀገር ለመጨመራቸው ምክንያት የሆነው ደግሞ፤ ዜጎች የተመጣጠኀ ምግብ አለማግኘታቸው፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ አለማድረጋቸውና ሲጋራ አዘውትሮ ማጨስ ዋነኞቹ ናቸው ሲሉ ሚኒስትር ዲኤታው ለአሐዱ ተናግረዋል።

Post image

በእነዚህ ምክንያቶች ዜጎች ስር ለሰደደ የኩላሊት ህመም እንዲጠቁ ሆኗል፣ የልብና የደም ዝውውር መስተጓጎል ሰለባ ሆነዋል እንዲሁም ለስኳር፣ ለካንሰር እና ለአእምሮ ሕመመም በሽታ የሚጠቁት ዜጎች ቁጥርም ጨምሯል ብለዋል።

ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን በቀላሉ ማከም ይቻላል የሚሉት ሚኒስትር ዲኤታው፤ ችግር የሆነው ዜጎች በበሽታው ከተጠቁ በኋላ ራሳቸውን አግልለው ለብዙ ጊዜ ስለሚቀመጡ እስከ ሞት እያደረሰ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

መንግሥት ችግሩን ለመቅረፍ የአምስት ዓመት እቅድ ነድፎ እየሰራ መሆኑን በመግለጽም፤ በዚህ እቅድም ለበሽታው አጋላጭ ምክንያት የሆኑት ምንድን ናቸው? የሚለውን በመለየት፤ ከምንም በላይ ማህበረሰቡ ላይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ ይሰራል ብለዋል፡፡

በተጨማሪም በጤና ተቋማት እና ከጤና ተቋማት ውጭ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች የተጠቁ ዜጎችን በመለየት አስፈላጊውን የሕክምና ክትትል መስጠት እንዲሁም ማህበረሰቡ ቢያንስ በዓመት ሁለት ጊዜ ወደ ጤና ተቋማት በመሄድና ምርመራ በማድረግ ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች ነፃ መሆኑን ማረጋገጥ የሚችልበትን የአሰራር ስርዓት መዘርጋት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ