ጥቅምት 6/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) በአማራ ክልል ባለው የጸጥታና የሰላም እጦት ምክንያት ለተለያዩ ችግሮች ለተጋለጡ ዜጎች ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መንቀሳቀስ መቸገሩን የአማራ ክልል የሲቪል ማኅበረሰብ ሕብረት አስታውቋል።

በግጭቱ ሳቢያ በርካታ የመብት ጥሰቶች እየተፈጸሙ በመሆኑ፣ የእርዳታ አቅርቦቶችን በተገቢው መንገድ ተደራሽ ለማድረግ አስቸጋሪ ሆኗል ሲልም ሕብረቱ ገልጿል።

የክልሉ ሲቪል ማኅበረሰብ ሕብረት ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጋቱ ደስታ፤ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች እየተካሔደ ባለው ግጭት ምክንያት በተለይ የሕጻናት የመማር መብት፣ የዜጎች ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ እና ተገቢውን የጤና አገልግሎት የማግኘት መብት እየተጣሰ ነው ብለዋል፡፡

አክለውም፤ ለተለያዩ ችግሮች ለተጋለጡ ዜጎች ድጋፍ ለማድረግ ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያት፤ ድጋፍ ሰጪ ቡድኖች ለደህንነታቸው በመስጋት በየብስ ትራንስፖርት ተንቀሳቅሰው ከመስራት ይልቅ የአውሮፕላን ጉዞ መምረጣቸው የሰብአዊ ድጋፍ የማድረግ ሥራቸው ላይ ከፍተኛ እንቅፋት መፍጠሩን ለአሐዱ ገልጸዋል፡፡

በአማራ ክልል ያለው የሰላም እጦት ማኅበረሰቡን ለማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ለተለያዩ ችግሮች እየዳረገ በመሆኑ፤ የሚመለከተው አካል ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባም የሕብረቱ ዋና ዳይሬክተር አሳስበዋል።

በዚህም መንግሥት ከታጠቁ ኃይሎች ጋር በመነጋገር ወደ ምክክር እና ድርድር እንዲመጡ የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል።

በተለይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዲከበርና በሰላም ዙሪያ የሚሰሩ አካላት ልዩ ትኩረት በመስጠት ዘላቂ መፍትሔ መስጠት እንደሚገባው አጽንኦት ሰጥተዋል።

#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ