ሕዳር 26/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) የካፒታል ገበያ ስርዓት ትግበራ በኢትዮጵያ ውስጥ ከተጀመረ ገና ጥቂት ዓመታትን ያስቆጠረ ቢሆንም፤ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችን በመውሰድ የግብይት ስርዓቱን እያስተዋወቀና ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን አስታውቋል።

ዘርፉ በኢትዮጵያ ገና ብዙ ጊዜ ያልቆየ መሆኑን ያነሱት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሀና ተኸልቁ፤ በእነዚህ አጭር ጊዜያት ውስጥ ግን ገበያውን እንዴት እውን ማድረግ እንደሚገባና ከሌሎች ሀገራት ጋር ስለሚኖር ግንኙነት በርካታ ትምህርት መውሰድ መቻሉን ለአሐዱ ሬዲዮ ገልጸዋል።

Post image

በተለይም ከአፍሪካና ከዓለም አቀፍ ገበያዎች ልምድ መውሰድ መቻሉን ተናግረዋል።

በዚህ ሂደትም በዘርፉ ለሚደረግ ግብይት ኩባንያዎችን የማምጣትና የማማከር አገልግሎት ለመስጠት የተፈቀደው ለኢንቨስትመንት ባንኮች ብቻ እንደነበረ ያነሱት ዋና ዳይሬክተሯ፤ "ፈቃድ ሰጥተን ገበያውን ለማየት ስንሞክር ክፍተቱን ለይተናል" ብለዋል።

በዚህም መሰረት ከባንኮች በተጨማሪ መመሪያዎችን ተከትለው የሚሰሩ በቂ የሆነ ካፒታልና የሰው ሀይል ያላቸው ድርጅቶችም እንዲሳተፉ መደረግ መቻሉን ገልጸዋል።

ከዚህ ባሻገር በዘርፉ በርካታ አካላት የሚሳተፉ በመሆኑ የካፒታል ገበያ ልማትን የሚያመቻቹና የሚደግፉ ቴክኖሎጂዎችን የማስተዋወቅ እንዲሁም በተቋማት መካከል ትስስርና ውህደት መፍጠር አለመሆኑን አንስተዋል።

በአጠቃላይም አዲስ ስርዓትን ለመገንባት ጊዜ እንደሚወስድ ገልጸው፤ በፍጥነት ስርዓቱን ማስተዋወቅ ፈተና እንደነበረ ጠቁመዋል። በመሆኑም በኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ የሚፈለገውን ያክል ደረጃ ለመድረስ የሚሰራው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ዋና ዳይሬክተሯ ተናግረዋል።

#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ