ጥቅምት 7/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የዲያስፖራ ማኅበረሰብ አጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት በስኬት መጠናቀቁን በዛሬው ዕለት በሰጠው ሳምንታዊ መግለጫ አስታውቋል።

ኮሚሽኑ ለአጀንዳ ማሰባሰብ እና የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች በተለያዩ ስድስት አህጉራትና ሀገራት መዘዋወሩን፤ የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ አቶ ጥበቡ ታደሰ ገልጸዋል።

በተጨማሪም የዲያስፖራው ማኅበረሰብ በዋናው ጉባኤ ላይ የሚሳተፉ ተወካዮችንም መርጧል ብለዋል።

በውጪ ሀገራት በተካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ላይ አሜሪካ፣ እንግሊዝ እና ስዊድንን ጨምሮ ከፍተኛ ተቃውሞዎች ከአዳራሽ ውጪም በውስጥም እንደገጠሙት ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።

በተጨማሪም በኢትዮጵያ ሁለት ዜግነት እንዲኖር የሚጠይቅ አጀንዳ ከዲያስፖራው ማህበረሰብ ማቅረቡን ገልጸዋል።

በምክክሩ ሁሉም የዲያስፖራው አባላት መሳተፍ ባይችሉም፤ በቀጣይ በበይነመረብ (online) ሌሎችንም ለማሳተፍ እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።

ኮሚሽኑ በቀጣይ የሚሰራው ሥራ እስከ አሁን የተሰባሰቡ አጀንዳዎችን መቅረፅ እና ለጉባኤ ዝግጅት ማድረግ ነው ተብሏል።

ሆኖም ይህ ሂደት እንዲሳካ የትግራይ ክልል አጀንዳ ማሰባሰብ መጠናቀቅ እንዳለበት አቶ ጥበቡ ገልጸዋል።

ለዚህም ኮሚሽኑ ከፌዴራል መንግሥት እና ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር ፖለቲካዊ መፍትሄ እንዲሰጥበት እና ወደ ምክክር የሚገቡበትን መንገድ እየጠበቀ መሆኑን አስረድተዋል።

የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ እስከ ጥቅምት አጋማሽ ድረስ የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደቱ እንዲሳካ ጥረት እንደሚያደርጉ መግለጻቸውን ቃል አቀባዩ ጠቅሰዋል።

ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከ400 እስከ 500 የሚሆኑ ተሳታፊዎች የሚሳተፍበት ጉባኤ ለማዘጋጀት ሥራዎች እየተጠናቀቁ መሆኑን አቶ ጥበቡ ታደሰ አክለው ገልጸዋል።

‎#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ