ሕዳር 1/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) በሳዑዲ አረቢያ በተለያዩ እስር ቤቶችና ማቆያ ማዕከላት የሚገኙ ዜጎችን ከ17 ሺሕ በላይ ዜጎችን ከመስከረም 05 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በተሰራ ሥራ መመለስ መቻሉን የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡
ሚኒስቴሩ በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጿል፡፡

"ከውጭ ግንኙነት ቁልፍ ሥራዎች አንዱ የዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ ነው" ያለው ሚኒስቴሩ ፖሊሲውን በአግባቡ ለመተግበር በውጭ ሀገር የሚኖሩ ዜጎችን መብት ማስከበር፣ ለዜጎች ተገቢ የቆንስላ አገልግሎት መስጠት፣ በሄዱበት ሀገር ሕጋዊ የመኖሪያ ፍቃድ የሌላቸውና የሀገሩ መንግሥት ዜጎቻችን ሀገራቸውን እንዲለቁ ሲወስን መብታቸው፣ ክብራቸውና ደህንታቸው ተጠብቆ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል።
በዚህም መሠረት ባለፉት አራት ዓመታት በተለያዩ የመካከለኛ ምሥራቅ፣ የአፍሪካ እና እንደማይናማር ያሉ የእስያ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ከ500 ሺሕ በላይ ዜጎችንን ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ማድረግ መቻሉን አሐዱ ከሚኒስቴሩ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

እንዲሁም በሳዑዲ አረቢያ በተለያዩ እስር ቤቶችና ማቆያ ማዕከላት የሚገኙ ዜጎችን ከመስከረም 05 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ከ17 ሺሕ በላይ ዜጎቻችን መመለስ መቻሉን የገለጸው ሚኒስቴሩ፤ በአሁኑ ወቅትም ከሳውዲ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎቻችንን የመመለሱ ሥራ መቀጠሉን አስታውቋል።
በተመሳሳይ በየመን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ 36 ዜጎች ወደሀገራቸው እንዲመለሱ የተደረገ ሲሆን፤ ሌሎችንም አስፈላጊውን የሰነድ ማጣራት በማድረግ የጉዞ ሰነድ በማዘጋጀት ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት እንዲሁም ከዓለም ዓቀፉ የፍልሰተኞች ድርጅት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ መሆኑን ገልጿል።
በተጨማሪም በማይናመር፣ ላኦስ እና ካምቦዲያ እንዲሁም በሌሎች ሀገራት በተመሳሳይ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎችን የመመለስ ጥረቱ እንደቀጠለ ነው ብሏል።
ሆኖም ግን አሁንም ድረስ ዜጎች በተሳሳተ መረጃ በሕገ-ወጥ ደላሎች ተታለው ወደተለያዩ ሀገራት በመጓዝ ለእስራት እና ለሞት እየተዳረጉ መሆኑን የገለጸው የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር፤ ዜጎች ከሕገ-ወጥ ጉዞ ራሳቸውን እንዲከላከሉ እና እንዲጠነቀቁ አሳስቧል።
ወደ ውጭ ሀገራት የሚደረጉ ጉዞዎችና የሥራ ቅጥሮች በሕጋዊና መንግሥት ባስቀመጠው አሰራር ብቻ ሊሆን እንደሚገባ ጨምሮ ገልጿል።
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ