ሕዳር 3/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) የቀድሞው ሰላም ሚኒስቴር አቶ ታዬ ደንደአ ዛሬ በዋለው ችሎት በሁለቱ ክሶች ነጻ መባላቸውን ጠበቃቸው አበራ ንጉሥ ለአሐዱ ሬዲዮ ገልጸዋል።
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ጸረ ሽብር ችሎት በዛራ ውሎው፤ "ከጠላት ጋር መተባበር" በሚል በአንቀፅ 251(ሐ)፣ መገፋፋትና ግዙፋዊ መሰናዳት አንቀፅ 257(ሰ) እንዲሁም፤ የፀና ፍቃድ ሳይኖር የጦር መሳሪያ ይዞ መገኘት በሚል ሦስት ተደራራቢ ወንጀሎች ተከሰው በክርክር ሂደት ላይ እንደነበሩ ይታወቃል።
ይሁን እንጂ፤ የቀድሞ የሰላም ሚንስቴር ዴኤታ አቶ ታዬ ደንደአን መዝገብ ሲመረምር የነበረው 1ኛ የፀረ-ሽብር እና ሕገመንግሥታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ዛሬ ሕዳር 3 ቀን 2018 ዓ.ም. ባስተላለፈው ውሳኔ 'ተከሳሹ ከተጠረጠሩበት ወንጀል ነጻ ናቸው' ብሏል።

ጠበቃቸው አበራ ንጉሥ በሁለቱም የመጀመሪያ ክሶች ባቀረቡት የሰው፣ የሰነድ እና የቪዲዮ ማስረጃዎች በበቂ ሁኔታ ተከላክለዋል በማለት በአብላጫ ድምፅ በነፃ እንዲሰናበቱ ፍርድ መሰጠቱን የገለጹ ሲሆን፤ በ3ኛ ደረጃ ለቀረበባቸው የፀና ፍቃድ ሳይኖር የጦር መሳሪያ ይዞ መገኘት ወንጀል ግን 'ባቀረቧቸው ማስረጃዎች በበቂ ሁኔታ ማስተባበል አልቻሉም' በማለት የጥፋተኝነት ፍርድ በሙሉ ድምፅ ሰጥቷል ብሏል።
እንዲሁም ጥፋተኛ በተባሉት አንድ ክስ የቅጣት አስተያየት ለመስማት ለሕዳር 15 ቀን 2018 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል ሲሉ ጠበቃቸው አበራ ንጉስ ለአሐዱ ተናግረዋል።
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ