ጥቅምት 22/2018 (አሐዱ ሬዲዮ)የተባበሩት አረብ ኢምሬቶች (ዱባይ) ሀገር ተመዝግቦ የሚገኘውንና ዓለም አቀፍ የንግድ ምልክት የሆነውን "ሜድሶል አድቫንስድ ዲያግኖስቲክስ ማዕከል" በዛሬው ዕለት በኢትዮጵያ በይፋ ሥራ ጀምሯል፡፡
የጤና ሚኒስቴር ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትና የግሉ የጤና ዘርፍ ጋር በመተባበር ማዕከሉን ወደ ሀገር ውስጥ በማስመጣት፤ በአፍሪካ የመጀመሪያውን የሜድሶል ቼን ማስጀመራቸው ነው የተገለጸው።
ከተመሰረተ 40 ዓመታት እንዳስቆጠረ የተገለጸው ሜድሶል አድቫንስድ ዲያግኖስቲክስ ማዕከል ወደ ኢትዮጵያ መምጣቱ፤ ወደ ውጭ ሀገራት የሚላኩ የምርመራ ናሙናዎችን በሀገር ወስጥ ለማድረግ የሚያግዝ መሆኑ ተነግሯል።

ተቋሙ ከ3 ሺሕ በላይ የናሙና ምርመራዎችን ማድረግ እንደሚችል የገለጸ ሲሆን፤ ይህም በኢትዮጵያ ሕመም ካልተከሰተ ምርመራ ያለማድረግ ልምድን ለማስቀረት ያግዛል ሲሉ፤ የላብራቶሪው ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሱራፌል ሸዋ ታጠቅ ለአሐዱ ተናግረዋል።

ዓለም አቀፍ የንግድ ምልክት ነው የተባለው የላብራቶሪ አገልግሎቱ በዘርፉ በተሰማሩ ባለድርሻ አካላት ወደ ኢትዮጵያ ማስመጣታቸው ለሀገራችን የሕክምና ላብራቶሪ ፍላጎት ዓይነተኛ አማራጭ ከመሆንም ባሻገር፤ የደም ናሙናዎችን ወደ ሀገር ውስጥ በማስመጣትና በውስጥ አቅም በመስራት የላብላቶሪ አገልግሎት ለጎረቤት ሀገራትም ጭምር የመስጠት ኃላፊነት እንዳለበትም ተገልጿል።
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ