ሕዳር 4/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ መስለው በተለምዶ "ሿሿ” የተባለውን ወንጀል በመፈፀም ሞባይል ስልክ ሰርቀው ለማምለጥ ሲሞከሩ በተያዙ 7 ተጠርጣሪዎች ላይ የምርመራ ሤራው መቀጠሉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አስታውቋል፡፡

ተጠርጣሪዎቹ ናትናኤል አለሙ፣ አቤል ኮርሳ፣ ዕድላዊት መላከ፣ መቅደስ አቡሽ፣ ኢዛና ባህሩ፣ ፀጋ ታደሰ እና መቅደስ አምዴሳ የተባሉ ሲሆኑ፤ ሽፈራው ገበየሁ በተባለ ግለሰብ ላይ ወንጀሉን የፈፀሙት በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 ኮዬ ቂሊንጦ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ መሆኑ ተነግሯል፡፡

Post image

ከክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ተጠርጣሪዎቹ የሰሌዳ ቁጥር ኮድ 3- 89261 ኦ.ሮ በሆነ ሚኒባስ ተሽከርካሪ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ መስለው የግል ተበዳይን ጭነው እየተጓዙ ሞባይል ስልኩን ከኪሱ ከሰረቁ በኋላ፤ "ትራፊክ ይቀጣናል ጋቢና ግባ ብለው" እንዳስወረዱት እና ከወረደ በኋላ ጥለውት እንዳመለጡ ተገልጿል፡፡

በግል ተበዳይ ላይ ወንጀል እንደተፈፀመ የተመለከቱ የህብረተሰብ ክፍሎች እና ፖሊስ በጋራ ባደረጉት ክትትል ወንጀሉን ፈፅመዋል ተብለው የተጠረጠሩ 5 ሴቶች እና 2 ወንዶች ሳሪስ አቦ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ሲደርሱ ከተሽከርካሪው ወርደው ሊሰወሩ ሲሞክሩ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ነው ፓሊስ የገለጸው፡፡

Post image

በወቅቱ በተሽከርካሪው ላይ በተደረገ ፍተሻ ከተለያዩ ግለሰቦች ላይ በተመሳሳይ መልኩ የተሰረቁ ዘጠኝ ሞባይል ስልኮች መያዛቸውም ተነግሯል

በዚህም መሠረት የክፍለ ከተማው ፖሊስ መምሪያ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የጀመረውን የምርመራ ሥራ አጠናክሮ መቀጠሉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አስታውቋል፡፡

በተጠቀሰው ተሽከርካሪ እና በተያዙት ተጠርጣሪዎች 'ተመሳሳይ ወንጀል ተፈፅሞብኛል' የሚል ግለሰብ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በመቅረብ ከተያዙት ስልኮች መካከል የእሱ ንብረት ስለመኖሩ በማረጋገጥ እንዲወስድ እና ለፖሊስ ተጨማሪ መረጃ እንዲሰጥ ጥሪ ቀርቧል፡፡

#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ