መስከረም 19/2018 (አሐዱ ሬዲዮ) የአሐዱ ሬድዮ ሥራ አስኪያጅ፣ የታሪክ ተመራማሪና ጋዜጠኛው ጥበቡ በለጠ ከሴጅ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት የእውቅና ምስክር ወረቀትና ዋንጫ ተበርክቶለታል፡፡
ሴጅ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት በተለያዩ አጫጭር የሙያ ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በትላንትናው ዕለት አስመርቋል።
ከተመሠረተ 3 ዓመታትን ያስቆጠረው ሴጅ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት የጋዜጠኝነትና ኮሙዩኒኬሽን ትምህርት ዘርፍን ጨምሮ በ30 የትምህርት አይነቶች 380 ሰልጣኞችን ያስመረቀ ሲሆን፤ ከተመራቂዎች መካከልም ሕጻናት፣ ወጣቶች እና ጎልማሶች ይገኙበታል።

በዚሁ የምረቃ መርሐግብር ላይ የአሐዱ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆነውና በሙያው ለሀገር እና ለሕዝብ በርካታ አበርክቶት እያበረከተ ለሚገኘው ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ፤ የክብር ካባ በማልበስ ከኢፌዴሪ ባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ ነብዩ ባዬ (ረ/ፕ) እጅ የእውቅና ምስክር ወረቀት እና ዋንጫ ተበርክቶለታል።
ሚኒስቴር ዲኤታው በመድረኩ ባደረጉት ንግግር ይህ ሽልማት ጋዜጠኛ ጥበቡ በጋዜጠኝነቱ፣ በኪነ-ጥበቡ እና በታሪክ ምርምሩ ዘርፍ ለሀገሩ ላበረከተው አስተዋጽኦ የሚገባው መሆኑን ገልጸው፤ "ለወደፊቱም ጥሩ ማበረታቻ ይሆነዋል" ብለዋል።

የሴጅ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ታዲዎስ ምስጋናው በበኩላቸው፤ ማሰልጠኛ ተቋሙ ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ በዘርፉ ለሀገር ካበረከተው ከፍተኛ አስተዋጽኦ በመነሳት "ይህንን የእውቅና ሽልማት ሲሰጥ ከፍተኛ ኩራት ይሰማዋል" ብለዋል።
ሽልማቱን በክብር የተቀበለው ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ በበኩሉ፤ ለተበረከተለት ሽልማት ከፍተኛ ምስጋና በማቅረብ በቀጣይም በራሱ ፈቃድ የማሰልጠኛ ኢንስቲትዩቱ የክብር አምባሳደር ሆኖ እንደሚያገለግል ቃል ገብቷል።

ሴጅ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት በዘርፈ ብዙ የስልጠና ዘርፎቹ ላለፉት ዓመታት በማሰልጠን በሙያ ምዘና ብቃት አስመዝኖ በማብቃት ለገበያው ተወዳዳሪ የሆነ ባለሙያዎች በማበርከት ላይ የሚገኝ ተቋም መሆኑም በመድረኩ ተገልጿል።
#አሐዱ_የኢትዮጵያውያን_ድምጽ